Tuesday 9 April 2013

ከኮለኔል መንግስቱ እና ከአቶ መለስ ለኢትዮጵያ ሕፃናት አባት በመሆን ፋውንዴሽን ሊመሰረትለት የሚገባው ማነው?


Gudayachn Blog

“ጎዳና ቤቴ”
ሰኔ 25/2012 እአአቆጣጠር በቢቢሲ ድህረ ገፅ ላይ በወጣ አንድ ዘገባ መሰረት ኢትዮጵያ በአመት 5ሺህ በላይ ሕፃናት በማደጎነት ወደ አሜሪካ ብቻ እንደሚሄዱ እና አሜሪካ ከዓለም ላይ በማደጎነት ከምትወስደው ሕፃናትኢትዮጵያውያን ሕፃናት ከአምስቱ አንዱ እንደሆኑ ይገልፃል
አዲስ አበባ ብቻ ዛሬ ከመቶ ሺህ በላይ መግብያ ያጡ ”ጎዳና ቤቴ” ብለው አንቅልፍ በጣላቸው ቦታ ክልውስ ብለው የሚተኙ ሕፃናት ይኖሩባታል።ይህ የሆነው የኢትዮጵያ መንግስት ግዴለሽነት የመነጨ እንጂ ከድህነታችን ብቻ የሚመስለው ካለ ለመሳሳቱ እማኝ ላቅርብ።
ሕፃናት አሳዳጊ የሚያጡት ባብዛኛው የርስበርስ ጦርነት ሲኖር ወይንም ሰላም በተናጋበት ጊዜ ነው።ኢትዮጵያ ግን ጎዳና የወጡት ሕፃናቶቿ የበዙት በአንፃሩም ቢሆን ጦርነቱ ከቆመ ጊዜ ጀምሮ ነው ለምን?
በ1969 ዓም በዚያድባሬ ሱማሌ ወረራ ሳቢያ ብዙ ሕፃናት አባት እናታቸውን አጡ።ሀገሪቱ በወቅቱ ገንዘብ የላትም።ምዕራባውያን ፊታቸውን አዙረውባት ነበር።ግን ሕፃናት ጎዳና አልተጣሉም ይልቁንም ኃላፊነት የተሰማቸው ኮለኔል መንግስቱ በ 16 ወራት ውስጥ የሕፃናት አምባ እንዲገነባ አድርገው በአንድ ጊዜ ከአምስት ሺህ ሕፃናት በላይ የሚይዝ ትልቅ የሕፃናት ማሳደግያ በአፍሪካ በግዙፍነቱ (በውቅቱ) እና በአቅሙ ቀዳሚ ሆኖ ተገንብቷል። ኢህአዲግ መንግስት ከሆነበት ጊዜ ጀምሮ ሲያዳክመው ቆይቶ በ 1990 ዓም ተዘጋ። ኢህአዲግ ወያኔ የነበረውን አስፋፍቶ ሕፃናትን ከጎዳና ኑሮ ከማዳን ይልቅ ሕፃናትን በማደጎነት እየሸጠ በአንድ ሕፃን በትንሹ 25ሺህ ዶላር መሰብሰብ እና ወደኪሱ ማስገባቱን መረጠ።

ከኮለኔል መንግስቱ እና ከአቶ መለስ ለኢትዮጵያ ሕፃናት አባት በመሆን ፋውንዴሽን ሊመሰረትለት የሚገባው ማነው?
ዛሬ ኮለኔል መንግስቱ እንደጀመሩት ቢቀጥል ኖሮ በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሕፃናት በተማሩበት እና ከጎዳና ኑሮ በዳኑበት ነበር። ሃቁ ይህ ነው።አዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ላይ የተሰቀለው ቢል ቦርድ እና ኢቲቪ በአቶ መለስ የሞቱ ሰሞን ከዜና አንባቢው ጀርባ አቶ በለስ ጣታቸውን ወደ ሕፃናት ሲዘረጉ ያሳያል።ግን እንዴት ነው አቶ መለስ የኢትዮጵያ ሕፃናት አባት የሚባሉት? በምን መስፈርት? ሕፃናቱን ጎዳና ወድቀው እሳቸው በሚያልፉበት መንገድ በወታደሮቻቸው ስለገፏቸው ነው?ወይንስ የሕፃናት አምባን ስለዘጉላቸው? ነው ወይንስ በአስር ሺዎች በማያውቁት ባእዳን እጅ እንዲያድጉ ስለሸጧቸው። ‘መሸጥ’ የሚለው ቃል ለቀረበው ዕቃ ወይም ሰው አልያም ሕፃናት ገንዘብ ከፍሎ ሕፃኑን መውሰድ የሚለውን ትርጉም እስከያዘ ድረስ መሸጥ ከሚለው ቃል የትሻለ ሊገኝ አይችልም።
ቅዳሜ ጧት
ከአምስት አመት በፊት በ 2001ዓም አንድ ቅዳሜ ጧት ወደ ዝዋይ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም 45 ሰዎችን አሳፍሮ አንድ መለስተኛ አውቶቡስ መመናንን ይዞ መንገድ ላይ ነበር።በመንገድ ላይ በእድሜ ጎልማሳ ካህን ስለገዳሙ ታሪክ ይናገራሉ።በአንክሮ በመገረም ነበር የምንሰማው።እውነተኛ ታሪኩ ይህ ነበር።
“አቡነጎርጎርዮስ የዝዋይ ገዳም መስራች አንድቀን የመንፈስ ልጆቻቸውን እያስተማሩ ኮለኔል መንግስቱ ከአዋሳ ሲመጡ ጎራ ይላሉ።ወደ ገዳሙ ውስጥ ሳይገቡ ገና አጥሩን ሲመለከቱ በረጅሙ ታጥሮ ይመለከቱ እና ‘ይሄ መነኩሴ ይህን ይህል ቦታ አጥሮ አገሩ ታድያ ምን ተረፈ” ይሉ እና አንዱን ወታደር አቡነ ጎርጎርዮስን እንዲጠራቸው ይልኩታል። አቡነ ጎርጎርዮስ መልክቱ እንደደረሳቸው ‘አሁን ትምህርት ላይ ነኝ ደግሞስ ፈላጊ ይመጣል እንጂ ተፈላጊ እንዴት ይሄዳል?’ ብለህ ንገረው ብለው መልሰው ይልካሉ።ኮለኔል መንግስቱ እንዲህ አይነት ድፍረት በመስማታቸው ምንም ሳይሉ ወደ አዲስ አበባ ይመለሳሉ። በቀጣዩ ቀናት አቡነ ጎርጎርዮስ ኮለኔል መንግስቱን ቅሬታቸውን ለመንገር ይመጣሉ።ቅሬታቸው ሌላ ነበር።እንደገቡ አቡነ ጎርጎርዮስ በቁጣ “ለመሆኑ ሕፃናት አምባ የምታሳድጋቸው ልጆች አምላካቸውን ካላወቁ አውሬ እንደሚሆኑ ታውቃለህ?” ይሉታል ይደነግጣል። “ምን ይደረግ?” ይላቸዋል። “ለእኔ ፍቀድልኝ እኔ የማደርገውን አውቃለሁ” ይሉታል። ከድጋፍ ደብዳቤ ጋር ይልካቸዋል።
አቡነ ጎርጎርዮስ በህፃናት አምባ ውስጥ የቅዱስ ሚካኤል ታቦት አስይዘው በግቢው ውስጥ ለሕፃናቱ ቤተክርስቲያን ሰሩላቸው። ብዙ በስነምግባራቸው የታነፁ ሕፃናትን አፈሩ። በቀን በሚልዮን ብር ለጦርነት ታወጣ የነበረች ሀገር እንዲህ ልጆቿን ታሳድግ ነበር። ዛሬ የጎዳና ተዳዳሪ ሲበዛ መንግስት ኃላፊነት አይወስድም። ሕፃናቱን ለመሸጥ ግን ቢሮዎችን በየቦታው ባእዳን እንዲከፍቱ አርጎ የውጭ ምንዛሪ ማስገኛ አደረጋቸው። ቢቢሲ ከላይ በጠቀስኩት ቀን ላይ ባወጣው ዘገባ ላይ እንዲህ ይላል።
“በኢትዮጵያ የማደጎ ሕፃናትን ወደውጭ መላክ የንግድ ሥራ ሆኗል።ይህም ወደአሜሪካ ከመላው አለም ከሚገቡት ውስጥ ከአምስቱ አንዱን እጅ ይይዛሉ።ነገር ግን ይህ እንዴት ሞራላዊ ሂደት ሊሆን ይችላል?” በማለት ይጠይቃል። እውነት እንዴት ሞራላዊ ሂደት ሊሆን ይችላል?
ግን ከኮለኔል መንግስቱ እና ከአቶ መለስ ለኢትዮጵያ ሕፃናት አባት በመሆን ፋውንዴሽን ሊመሰረትለት የሚገባው ማነው?
ይህንን በኮለኔል መንግስቱ የተመሰረተውን ታሪካዊ የሕፃናት አምባ እንቅስቃሴ የሚያሳይ ፊልም ይመልከቱ እና ኃላፊነት የሚሰማው መንግስት ስጠን በሉ።
አበቃሁ
ጌታቸው
ኦስሎ

No comments:

Post a Comment