“በአስመሳይ ስደተኞች ላይ በቂ መረጃ አለ”
“ክፉን በክፉ መመከት ባያስደስትም ወቅቱ ያስገድደናል” ሲሉ የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር ኦባንግ ሜቶ በተለይ ለጎልጉል ተናገሩ። አገዛዙን ሸሽተው በተለያዩ አገራት ከለላ አግኝተው በስደት የሚኖሩም ሆኑ ጉዳያቸው እየታየ ያሉ ወገኖች አካሄዳቸውን እንዲያስተካክሉ አስጠንቅቀዋል።
የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣናትና ህግ አውጪዎች፣ የጀርመን የኢሚግሬሽን ሃላፊዎችና ከፍተኛ የፖለቲካ ሰዎች፣ ከኖርዌይ የኢሚግሬሽን ጉዳይ ሃላፊዎችና ተዛማጅ ሃላፊነት ካላቸው የህግ ክፍሎች፣ በካናዳ በተለያዩ ደረጃ ካሉ ባለስልጣናትና ወትዋቾች (አክቲቪስቶች)፣ በስዊድን አንዲሁም በእንግሊዝ በተመሳሳይ ግንኙነት ፈጥረው እየሰሩ መሆኑንን ያመለከቱት አቶ ኦባንግ “አገራቱ የስደት ፈቃድ ካገኙ በኋላ ለስደት ዳረገን ከሚሉት መንግሥት ጋር በቅርብ እየሰሩ ስላሉ አስመሳይ ስደተኞች አስገራሚ መረጃዎች መሰብሰባቸውን አውቃለሁ” ብለዋል።
አቶ መለስ በሞቱ በወር ጊዜ ውስጥ ብቻ በካናዳ ቫንኮቨር 27 አንድ አይነት ቋንቋ ብቻ የሚናገሩ ወጣቶች ጥገኛነት መጠየቃቸውን ጉዳዩን በጥብቅ እየመረመሩት ካሉ ክፍሎች ማረጋገጣቸውንና የምርመራውን ውጤት በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ ያመለከቱት አቶ ኦባንግ፣ “ወጣቶቹ ካናዳ የገቡት ለእያንዳንዳቸው 75 ሺህ ዶላር በማውጣት ነው። ይህን ገንዘብ ማን ሰጣቸው? እንዴት አገኙት? እንዴት ከአንድ አካባቢ (ክልል) ብቻ ሊሆኑ ቻሉ? የሚሉት ጉዳዮች ምርመራውን በያዙት ወገኖች ላይ ግራሞት የፈጠረ ትልቅ ጉዳይ ነው” በማለት የጉዳዩን አሳሳቢነት ከገንዘብ ማሸሽ ጋር በማያያዝ አመላክተዋል። ለምሳሌ አንድ ጉዳይ አነሱ እንጂ በመላው ካናዳ በተመሳሳይ የምርመራ ስራ እየተሰራ መሆኑንን ተናግረዋል።