Tuesday 23 September 2014

በጋምቤላ ግጭት የተጠረጠሩ ባለስልጣናት በቁጥጥር ስር እየዋሉ ነው


ሸፍተው የነበሩ የዞኑ የፖሊስ ልዩ ሃይል አዛዥና የሚሊሽያ አባላት እጃቸውን ሰጡ
በጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በጎደሬ ወረዳ፣ በመዠንገር ዞን በተቀሰቀሰውና አሁንም ድረስ በአንዳንድ ቦታዎች በቀጠለው ግጭት እጃቸው እንዳለበት የተጠረጠሩ የክልሉ ባለስልጣናት ያለመከሰስ መብታቸው ተነስቶ በቁጥጥር ስር እየዋሉ ነው፡፡ በአዲስ አመት ዋዜማ የተቀሰቀሰውና ከ40 በላይ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈው ግጭት መነሻ ከመሬት ባለቤትነት ጋር የተያያዘ እንደሆነ ለአዲስ አድማስ የገለፁት ምንጮች፤ “ደገኞች መሬታችንን ይልቀቁ” የሚሉ የአካባቢው ተወላጆችና አንዳንድ የክልሉ ባለስልጣናት በመንግስት ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን የሰፈራ ፕሮግራም ተገን በማድረግ ነባር ይዞታ ያላቸውን ነዋሪዎች በማፈናቀላቸው ግጭቱ መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡
በአካባቢው ተወላጆችና ከሌሎች አካባቢዎች በመጡ ነዋሪዎች መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየና በየጊዜው የሚያገረሽ ግጭት እንዳለ የሚታወቅ ሲሆን፣ በቅርቡ የተከሰተው ግጭት ሊቀሰቀስ እንደሚችል የፌደራል መንግስት በደረሰው መረጃ መሰረት፣ በአፈ ጉባኤ ካሳ ተክለብርሀን የተመራ ቡድን ከክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር በመተባበር በአካባቢው የማረጋጋት ስራ ቢሰራም፣ በዞኑ ያሉ አንዳንድ የፖሊስና የሚሊሺያ አባላት “መሬታችንን ይልቀቁ” የሚለው ሃሳብ እንዲሰርፅ በማድረጋቸው ግጭቱ እንደተፈጠረ ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡
ግጭቱ ከተፈጠረ በኋላም የዞኑን የፖሊስ ልዩ ሀይል አዛዥ ጨምሮ የፖሊስና የሚሊሽያ አባላት ሸፍተው ጫካ መግባታቸውን የተናገሩት ምንጮች፤ በአሁኑ ወቅት አዛዡና ሌሎች ጥቂት አባላት እጃቸውን ለመንግስት ሃይሎች እንደሰጡ ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የተከሰተው ግጭት ሁነኛ መፍትሔ ካልተበጀለት፣ በአቅራቢያ ወደሚገኙ ሌሎች አካባቢዎች ሊዛመት ይችላል የሚል ከፍተኛ ስጋት መፈጠሩን ያመለከቱት ምንጮቹ፤ ከወራት በፊት ማንነታቸው ያልታወቀ የታጠቁ ሰዎች ዲማ ተብሎ በሚጠራው የክልሉ አካባቢ አስር ሰላማዊ ዜጎችን ገድለው መሰወራቸውን ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የተከሰተው ግጭት ከክልሉ የፀጥታ ሃይሎች ቁጥጥር በላይ በመሆኑ፣ የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሃይል ጣልቃ ገብቶ የማረጋጋት ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በተከሰሱ መፅሄቶች ላይ ውሳኔ ለመስጠት ፍ/ቤት ኦሪጂናል መፅሄቶች እንዲቀርቡለት አዘዘ


በ“አዲስ ጉዳይ”፣ በ“ሎሚ” እና በ“ፋክት” መፅሄት አሳታሚዎችና ሥራ አስኪጆች ላይ ለተመሰረቱት የወንጀል ክሶች የቀረቡት ማስረጃዎች ከየመፅሄቶቹ ገፆች የተቆራረጡና ኮፒ የተደረጉ መሆናቸውን የጠቆመው ፍ/ቤት፤ አቃቤ ህግ ኦርጂናል መፅሄቶችን በማስረጃነት እንዲያቀርብ ትዕዛዝ በማስተላለፍ ለፍርድ ውሳኔ በድጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ፡፡ ፍ/ቤቱ ከትላንት በስቲያ በዋለው ችሎት አቃቤ ህግ ከጥቅምት 3 በፊት ኦሪጂናል መፅሄቶችን በማስረጃነት እንዲያቀርብ አዟል፡፡ የ“አዲስ ጉዳይ” መፅሄት አሳታሚ ሮዝ አሳታሚና ስራ አስኪያጁ አቶ እንዳልካቸው ተስፋዬ፣ የ“ሎሚ” መፅሄት አሳታሚ ዳዲሞስ ኢንተርቴይመንትና ፕሬስ ስራዎችና ስራ አስኪያጁ አቶ ግዛው ታዬ እንዲሁም የ“ፋክት” መፅሄት አሳታሚ ኢንተርቴይመንትና የፕሬስ ስራዎች ኃ/የተ/የግ/ማህበርና ስራ አስኪያጅ ፋጡማ ኑርዬ በጋዜጣ ጥሪ ተደርጎላቸው ባለመቅረባቸው ጉዳያቸው በሌሉበት እየታየ ሲሆን በተለያዩ ጊዜያት ታትመው በወጡ መፅሄቶቻቸው ሃሰተኛ ወሬዎች በማውራት፣ ለአመፅ የሚያነሳሱ ፅሁፎችን ለህዝብ በማድረስ፣ በህገ መንግስቱና በህገ መንግስታዊ ስርአቱ ላይ አመፅ ለማስነሳት ሞክረዋል የሚሉ ክሶች እንደቀረበባቸው ይታወሳል፡፡ ከ“ፋክት” መፅሄት አሳታሚ ድርጅት ስራ አስኪያጅ በስተቀር የሁሉም ተከሳሽ መፅሄቶች ሥራ አስኪያጆችና ባለቤቶች አገር ለቀው መውጣታቸው ይታወቃል፡፡

Tuesday 2 September 2014

ፑንትላንድና ሶማሌላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የመዋሃጃ ሰነድ አቀረቡ

ሰነዱ አሜሪካንን ጨምሮ ለኃያላን አገሮች ቀርቧል

puntland somaliland


ራሳቸውን ራስ ገዝ አገር አድርገው በማስተዳደር ላይ ያሉት ሶማሌላንድና ፑንትላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ውህደት ለመፈጸም የሚያስችላቸውን ሰነድ ለአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መ/ቤት (ስቴት ዲፓርትመንት) ማቅረባቸው ተሰማ። ሰነዱ ለእንግሊዝና ለሌሎች የአውሮፓ ሃያል አገራት መቅረቡም ታውቋል። ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ ክፍሎች “እንሰጋለን” ሲሉ የውህደት ጥያቄው ሊተገበር የሚገባው እንዳልሆነ አመልክተዋል
ከኢትዮጵያ ጋር ለመዋሃድ ጥያቄ ያቀረቡት ሁለቱ የሶማሌ ጠቅላይ ግዛቶች የተጠቀሰውን ሰነድ ማቅረባቸውን የተናገሩት የጎልጉልምንጮች፣ የሰነዱን ዝርዝርና ውህደቱ በምን መልኩ ሊከናወን እንደሚችል ዝርዝር መረጃ ለጊዜው ከመስጠት ተቆጥበዋል።
ፑንትላንድና ሶማሌላንድ ራሳቸውን ከተበጠበጠችው እናት አገራቸው ነጥለው አገር ማስተዳደር ከጀመሩ ዓመታት ቢያስቆጥሩም እስካሁን ድረስ በአገርነት እውቅና አላገኙም። በዚህ መነሻ ይሁን በሌላ፣ ሁለቱ የሶማሌ ጠቅላይ ግዛቶች ኢትዮጵያን እናት አገራቸው ሆና እንድታስተዳድራቸው ሰነድ አዘጋጅተው ከማቅረባቸው በፊት ከኢህአዴግ ጋር ረዘም ላለ ጊዜ ሲመክሩ ቆይተዋል።